Tuesday 14 August 2012

ድምፃችን ይሰማ

Thursday, August 2, 2012ድምፃችን ይሰማበአላህ ስም እጅግ በጣም ሩህሩህ በጣም አዛኝ በሆነውየተከበራችሁ ሙስሊሞች፤ይህንን የምንፅፍላችሁ ዛሬ በኤፍ ኤም ሬዲዮ ተላልፎ የነበረውን የ‹‹ሽማግሌዎች›› እና የፖለቲከኞች ውይይትን ተከትሎ በብዙሃኑ ውስጥ የተፈጠረውን የስሜት መደበላለቅ እኛም ተጋርተነዋልና የበኩላችንን ለማለት ነው፡፡በእርግጥ ሽምግልና የተቀደሰ ተግባር ነው፡፡ ዛሬ ላይ በሽምግልና ተሰይመው ያገኘናቸው ግለሰቦች ከፊሎቹ የምናውቃቸውና የምንወዳቸው፤ ከፊሎቹ ደግሞ የማናውቃቸውና የምንወዳቸው ሲሆኑ መነሻቸው ሽምግልና ከሆነ እሰየው፤ ይበሉ ያስብላል፡፡ ምክንያቱም ከፀብ ይልቅ እርቅ እጅጉን የተሸለ ነውና፡፡ በእርግጥ እኛ ከማንም ጋር ፀብ ውስጥ አልገባንም ይልቁንም ሰላማዊ የመብት ጥያቄአችንን ወደ ፀብና ግርግር ለመቀየር ተሴረብን እንጂ፡፡ በዛሬው ፕሮግራም እጅግ በርካታ ነጥቦችን ለመረዳት በመቻላችን በነዚህ ‹‹ሽማግሌዎች›› አማካኝነት ይሄ መድረክ መመቻቸቱ ከመልካም ቆጠርነው፡፡ እነዚህ ሽማግሌዎች በመኖራቸው እኮ የምንወዳቸው ኮሚቴዎቻችን ቢያንስ በአካላዊ ደህንነት በህይወት መኖራቸውን ተረዳን፤ ተጋብዘውም ይሁን በራስ ተነሳሽነት በዚህ ቀውጢ ሰአት ቢያንስ ይህ ነገር ወዴት እየሄደ ነው ብለው ለመጠየቅ የደፈሩና ሰሚ ያገኙ ሰዎች እንዳሉን አወቅን፤ ምርጫው የሙስሊሞች እንደመሆኑ መጠን መስፈርቱም ሙስሊሞች መሆን ብቻ እንጂ ተጨማሪ ታፔላ ሊኖረው እንደማይገባ ሰማን፤ በተጨማሪም ህዝበ ሙስሊሙን ለፀሃይና ለዝናብ አጋልጦ ለስምንት ወራት ከአደባባይ ያዋለው ምክንያት የቤቱና የሃይማኖቱ ጉዳይ እንጂ ሌላ ድብቅ አጀንዳ አለመኖሩን ከዚህ ሁሉ ፉከራ በኋላ እነዛው ያስገረፉን ‹‹መሪዎቻችን›› አመኑ፡፡ ምርጫውን በቀበሌ ማካሄድ እና በመስጂድ ማካሄድ የህዝበ ሙስሊሙ ምርጫ መሆኑንም የፖለቲካ መሪዎቻችን ለሚዲያ ፍጆታ ሲሉ ቢሆንም ዳግም አረጋገጡልን፡፡ ታዲያ ይህን የቤታችንን ጉዳይ ለማስተካከልና ምርጫችንን በመስጂዳችን ለማድረግ መታገል የኛ ፋንታ እንጂ የፖለቲከኞች ወይንም የሽማግሌዎች አይደለም፡፡ሽምግልና መሰረታዊ ሃሳቡ በሁለት ወገን ያሉ አለመግባባቶችን ከስር መሰረቱ በመመርመር ‹‹አንተም ተው›› ‹‹እናንተም ተዉ›› በሚል ገለልተኛ ሃሳብ ማማከር እንጂ የአንደኛውን ወገን ሃሳብ ከነእንክርዳዱ ሌላኛው እንዲቀበል ተፅእኖ መፍጠሪያ አይደለም፡፡ በኛ እምነት የዛሬው ውይይት የሽምግልና ሂደቱ መጀመሪያ እንጂ የውሳኔ ሃሳብ የቀረበበት አይደለም፡፡ ህዝብ እኮ ክቡር ነው፡፡ የተከበረ ህዝብ ደግሞ በጉዳዩ የመሳተፍና የመወሰን መብት አለው፡፡ እናም በራስ ተነሳሽነት የተሰባሰቡ ሽማግሌዎች አማራጭ ሃሳቦችን ሊያመነጩ እንጂ በህዝብ ስም የድምዳሜ ሃሳብ ሊያቀርቡ አይችሉም፡፡ በቀጣይ ወደ ህዝብ ወርደው የልቡን ትርታ በማዳመጥ ሁሉን የሚያስማማ መፍትሄ ያቀርባሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ የስምንት ወራት በመላው አለም የሚገኝ ሙስሊም ያደረገው የበሰለ፤ የሰከነነ እና አላማውን ጠንቅቆ ያወቀ የመብት ፍለጋ ትግል ምክንያታዊ የሚለው ቃል ቢያንሰው እንጂ ዛሬ እንደሰማነው በስሜት የተነዳ ምክንያት የለሽ ግርግር አይደለም፡፡ የምርጫችን በመስጂዳችን መፈክርም ቃሉ ስላማረ የተዘመረ ሳይሆን በመርህ ደረጃም ብቸኛ አማራጭ በመሆኑ ለአተገባበርም ይህን ማሳካት የሚችሉ ያገር ልጆች እንዳሉ በመተማመን ከበቂ ጥናትና ትንተና ጋር የተቀመጠ ነው፡፡ እኛ ያጣነው ድምፃችንን የሚሰማ እና አማራጭ ሃሳባችንን ‹‹እስኪ እንዴት ተደርጎ ወደትግበራ ሊገባ ይችላል›› ብሎ የሚያዋየን እንጂ መፍትሄው ከመፈክሩ የቀለለ እንደሆነ እናምናለን፡፡ በመሆኑም የተጀመረውን የሽምግልና ሂደት እያደነቅን ጉዳዩ የህዝብ እንደመሆኑ መጠን ውሳኔውም የህዝብ እንደሆነ ልናሰምር እንወዳለን፡፡ በመጨረሻም ሚኒስትረ ዴኤታው እንዳስቀመጡት ለሁሉም ነገር ቅድመ ሁኔታው የአንዋርና የአወሊያ ህዝብ ወደቤቱ መመለስ አይደለም፡፡ ብሶት ፈንቅሎት አደባባይ የወጣው በመላው አለም የሚገኝ ኢትዮጵያዊ ሙስሊም እንጂ የአዲስ አበባ ሰው ብቻ አይደለም፡፡ ዛሬ ለይስሙላ መፍትሄ ወደቤቱ ቢገባም የፍትህ እጦት ዳግም ከመስጂድም አልፎ አደባባይ ሊያወጣው እንደሚችል አጥተውም አይደለም፡፡ ለግዚያዊ ችግር ተብሎ ግዚያዊ መፍትሄ ላይ ማተኮር ዘላቂ ውጤት አያመጣምና የኡለማዎች ምክር ቤት አካሂደዋለሁ የሚለውን የህግ አግባብ የሌለው የሩጫ ምርጫ በመግታት ጉዳዩ ሰከን ተብሎ እንዲጤን እንመክራለን፡፡ የሰላም አምባሳደር ተብለው ሊሸለሙ የሚገባቸው ውድ ኮሚቴዎቻችንን እና የወከልናቸውን እኛን ሚሊዮኖች ህገወጥ እያሉ ህዝብን ወደቤትህ ግባ ማለት ለማንም አይበጅምና ቅድመ ሁኔታው የህገመንግስቱ መከበርና የፍትህ መስፈን ይሁን እንላለን፡፡ አላህ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ሰላም ያድርግ!!!Posted by bilal Ethio at 3:27 PM

No comments:

Post a Comment